የተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች መንግስት የመኖሪያ ቪዛ ሕግጋትን ተላልፈው ለሚኖሩ የውጭ ሀገር ዜጎች የሁለት ወር የእፎይታ ጊዜን የሚሰጥ የምህረት አዋጅ ይፋ አድርጓል።
 
የተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች መንግስት የዜግነትና ኢሚግሬሽን ባለስልጣን እ.ኤ.አ. ኦገስት 1 ቀን 2024 ባወጣው መረጃ መሰረት የመኖሪያ ቪዛ ሕግን ተላለፈው ለቆዩ የውጭ ሀገራት ዜጎች የመኖሪያ ቪዛቸውን ከቅጣት ውጪ ለማስተካከል ወይም ሀገሪቷን ለቀው ለመውጣት እንዲችሉ እ.ኤ.አ ከሴፕቴምፐር 1 ቀን 2024 ጀምሮ እስከ ኦክቶበር 30 ቀን 2024 ለሁለት ወራት የሚቆይ የእፎይታ ጊዜ እንደሚሰጥ አሳውቋል።
ስለሆነም በቀጣይ ከምህረት አዋጁ አፈጻጸም ጋር የተያያዙ ዝርዝር የአፈጻጸም ጉዳዮች በቀጣይ እንደሚያወጣ የገለጸ በመሆኑ መመሪያው ሲወጣ የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን። በተጨማሪም የወጣውን አዋጅ ተከትሎ የተለያዩ የሀሰት መረጃዎችን በማህበራዊ ሚዲያም ሆነ በሌሎች መንገዶች ከሚያስተላልፉ ማንኛውም አካላት ጥንቃቄ እንድታደርጉ ስንል በጥብቅ እናሳስባለን።
 
በመጨረሻም ዜጎቻችን ከዚህ በታች ለተጠቀሱት ጉዳዮች ትኩረት በመስጠት ከወዲሁ ዝግጅት እንድታደርጉ እናሳስባለን።
1. ከዚህ ቀደም ፓስፖርታችሁ ታድሶ መጥቶላችሁ ያልወሰዳችሁ እንዲሁም ከተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የኢሚግሬሽንና ፖሊስ ተቋማት ከየቦታው ተሰባስበው ወደ ቆንስላችን የተመለሱ ፓስፖርቶች ዝርዝራቸውን በድጋሚ ምናሳውቅ በመሆኑ እየቀረባችሁ እንድትወስዱ፣
2. የፓስፖርታችሁ የመጠቀሚያ ጊዜ የተጠናቀቀ ወይም ስድስት ወር የቀረው ከሆነ እንዲሁም ሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሌላችሁ ከሆነ ከነገ ሐምሌ 26 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤታችን እየቀረባችሁና ማሟላት የሚገባችሁን መስፈርቶች እያሟላችሁ ፓስፖርታችሁን እንድታድሱ እናሳስባለን።
3. ፓስፖርታችሁ የጠፋባችሁ ወይም ሰነድ አልባ የሆናችሁ ዜጎች ትክክለኛ ወይም ሕጋዊ የፓስፖርት ኮፒ ይዛችሁ በመቅረብ ፓስፖርታችሁን ማደስ የምትችሉ መሆኑን እንገልጻለን።
4. ፓስፖርትም ሆነ የፓስፖርት ኮፒ የሌላችሁ ዜጎች በምን መንገድ የአዋጁ ተጠቃሚ መሆን እንደምትችሉ በቀጣይ የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን።

Disclaimer: The official text of the Embassy Website is the English language version. Any discrepancies or differences created in translations are not binding and have no legal effect for compliance or enforcement purposes.

X
Twitter
Facebook
YouTube
Instagram