ክቡር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ በተገኙበት የዜጎች መረጃና አገልግሎት አስተዳደር (CISMS) መተግበሪያ ተመረቀ።
 
በዱባይና ሰሜን ኤምሬቶች የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤት ከኢትዮጵያውን ኮሙኒቲ ማህበር ጋር በመተባበር የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ እና የአሠራር ስርዓት በማዘመን ሥራዎች በ“Automation” ተደግፈው እንዲስጡ እና የዜጎች የተሟላ መረጃ ምዝገባ እንዲጀመር፣ እንዲሁም የፖስፖርት ዕድሳት፣ የሰነድ ማረጋገጥ፣ የዉክልና አሰጣጥ፣ ለዳያስፖራ ድጋፍ፣ የቢዝነስ ዲፕሎማሲ እና በሌሎችም የሚሰጡ አገልግሎቶች ቀልጣፋ እና ውጤታማ እንዲሆኑ ለማስቻል የ “Citizens Information and Services Management System” /CISMS/ መተግበሪያ ለምቶ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል።
በመሆኑም አዲስ የለማው የ “Citizens Information and Services Management System” /CISMS/ መተግበሪያ ዛሬ ክቡር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ በተገኙበት በዛሬዉ ዕለት ሐምሌ 1 ቀን 2015 ዓ.ም በይፋ ተመርቋል። በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ በዱባይና ሰሜን ኤምሬቶች የኢፌዲሪ ቆንሱል ጄኔራል ክቡር አምባሳደር አክሊሉ ከበደን ጨምሮ ዲፕሎማቶች፣ የኢትዮጵያዉያን ኮሚኒቲ ማህበር የአመራር ቦርድ አባላት የኮሙኒቲ ማህበር ጽ/ቤት አመራሮች እና ሠራተኞች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ በዱባይና ሰሜን ኤምሬቶች የሚኖሩ የዳያስፖራ አባላት ተገኝተዋል።
 
ክቡር አምባሳደር አክሊሉ ከበደ ባደረጉት የመግቢያ ንግግር ቆንስላ ጄኔራሉ ለተገልጋይ ዜጎች የሚሰጠዉን አገልግሎት ለማዘመንና የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስጠበቅና አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የሚረዳ አዲስ የመተግበሪያ ሲስተም ተግባራዊ ለማድረግ በኮሚኒቲ ማኅበሩ የፋይናንስ ድጋፍ ላለፉት አስራ አንድ ወራት በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዉ፤ አሁን ተግባራዊ የሆነዉ ሲስተም የዜጎችን መረጃ በመያዝ፣ የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት እንዳስቻለ ገልጸዋል። በዚህም መሠረት ባለፉት ጥቂት ወራት የ 20ሺህ ዜጎች መሠረታዊ መረጃ መያዙን እና ይህም በርካታ ችግሮችን ለመፍታት ያስቻለ መሆኑንም ገልጸዋል።
ክቡር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ አዲስ የለማውን የ “Citizens Information and Services Management System” /CISMS/ ሶፍትዌር በይፋ በመረቁበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት ቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤትና ኮሚኒቲ ማኅበሩ የዜጎች አገልግሎት አሰጣጥን የተቀላጠፈ ለማድረግ ሶፍት ዌሩን በማልማታቸው ያላቸውን አድናቆት ገልፀው ለወደፊቱ እስከ ሀገር ቤት ከተለያዩ ባለድርሻ ተቋማት ጋር በጋራ የተቀናጀና የተናበበ ሥራ መሥራት እንዲቻል በዋናው መ/ቤት በኩልም ዕገዛ እንደሚደረግ ቃል ገብተዋል።
በተያያዘም ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው የተጀመረው አውቶሜሽን እየዳበረ እና እየተጠናከረ መሄድ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
 
በመጨረሻም ሶፍት ዌሩን በማልማት ሂደት ውስጥ በክቡር ቆንስል ጄኔራሉ በሚመራው የለውጥ ማነጅመንት ኮሚቴ ውስጥ አባል በመሆን ከፍተኛ አስተዋፅጾ ላበረከቱ የኮሙኒቲ ማህበር የአመራር ቦርድ አባላትና ዲፕሎማቶች፣ ለኮሙኒቲ ማህበር ጽ/ቤት እና ለማህበሩ ጽ/ቤት ባለሙያዎች የምስጋና የምስክር ወረቀት የተበረከተ ሲሆን በዱባይና ሰሜን ኤምሬቶች የኢፌዲሪ ቆንስላ ጽ/ቤት እና የኢትዮጵያውን ኮሙኒቲ ማህበር በጋራ ያስለሙትን መተግበሪያ ያለማው TATATECH, TECHNOLOGY PRODUCTS & EDUCATION” በዱባይ የሚንቀሳቀስ ኢትዮጵያዊ ኩባንያ የዕውቅና ሽልማት ተበርክቶለታል።
AmharicArabicEnglish

Disclaimer: The official text of the Embassy Website is the English language version. Any discrepancies or differences created in translations are not binding and have no legal effect for compliance or enforcement purposes.

X
Twitter
Facebook
YouTube
Instagram